ኑሮ በአዲስ አበባ

ነፃነት ዘለቀ (ከአዲስ አበባ)
ትናንት ሲያቀብጠኝ ከአንድ ጓደኛየ ሞባይል እነዚያ አይሲስ የሚባሉ ጉግማንጉጎች እነዚያን 21 ክርስቲያን የግብፅ ዜጎች በሊቢያ አንድ የባሕር ዳርቻ ላይ አንገታቸውን ሲቀሉ የሚያሣይ ቪዲዮ አየሁ – እስከመጨረሻው መዝለቅ አልቻልኩምና ግን ዋናው ባራኪ በግራ እጁ የያዘውን ጩቤ ወደ እኛ ወደተመልካቾቹ ዘርግቶ እያስፈራራ ሲዝት አጠፋሁት።
የሰው ልጅ በሰው ልጅ ላይ እስከዚህ መጨከኑ የሚያመላክተን ዋና ቁም ነገር የዚች ምድር ሰዎች የደረስንበት አጠቃላይ መንፈሣዊና ኅሊናዊ ኪሣራ ሊቀለበስ ወደማይችል ከፍተኛ የመጨረሻ ደረጃ መድረሱን ነው። ለምግብነት የተፈቀዱልንን እንስሳት እንኳን ስናርድ የሚዘገንነንና በዚህም ምክንያት የማናርድ ብዙ እንስፍስፍ ሰዎች አለን። ሰውን የሚያህል ክቡር ፍጡር ሊያውም በሚከተለው ኃይማኖት ምክንያት ብቻ በስለት አንገቱን ቀንጥሰው ጀርባው ላይ ሲያስቀምጡ ሊሰቀጥጣቸው ይቅርና በደስታ የሚፈነጥዙ “ሰዎች”ን በዚህ በ21ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ስናይ በሰዎች ተፈጥሮ መለያየት እጅግ እንገረማለን።
“A Message Signed with Blood, to the Nation of the Cross” ይላል የቪዲዮው መግቢያ። አስፈሪ ነው። እነዚህ ሰዎች በያዙት የመስፋፋት ሂደት ከቀጠሉ ሌሎቻችንም ይህ አስቀያሚ ዕጣ የሚቀርልን አይመስለኝም። ነገሩ “የፋሲካው በግ በገናው በግ ይስቃል” እንዳይሆን ያሰጋል – እየሆነም ነው እንጂ፤ ከመካከለኛው ምሥራቅ የተነሣ እሳት አፍሪካ ጫፍ ሊቢያና የመን ሲደርስ አያድርስ ብሎ ከመጸለይ ውጪ እኛስ ምን ዋስትና አለን? ይህን ቪዲዮ ከተመለከትኩ በኋላ ለረዥም ጊዜ ሥራየን በአግባቡ መሥራት አልቻልኩም። ሰው ሆኖ የመፈጠር ዕዳ የቀሰቀሰብኝ የተስፋ መቁረጥ ስሜት መላ ሰውነቴን ወረረው – በአካልም፣ በመንፈስም፣ በኅሊናም እየኮሰመንኩ ስሄድ በምናቤ ይታየኝ ጀመር። አለመፈጠሬን የመረጥኩበት አንዱና ትልቁ አጋጣሚ ይህን ዘግናኝ ቪዲዮ በከፊልም ቢሆን ያየሁ ጊዜ ነው።
ይህ በአስቀያሚነቱ ወደር የማይገኝለት ዓለም አቀፍ ክስተት በረድ እያለልኝ ሲመጣ ግን የአገራችን አይሲስ ነጋዴዎች ታወሱኝና ስለነሱ አብዝቼ መጨነቅን ያዝኩ፤ ሁለቱ ተመሳሰሉብኝ። ደረጃውና ዓይነቱ ይለያይ እንጂ ጭካኔ ሁሉ መጠሪያውም ሆነ ጎራው ያው ጭካኔ ነው። እነዚህ ኢትዮጵያውያን ኢይሲሶች የምላቸው በወያኔ የተፈጠሩ የዘመናችን ኅሊና ቢስ ነጋዴዎችንና ኑሯችንን ያመሰቃቀሉትን የሙስና አበጋዞችን ነው። ከወያኔ ቀጥለው የአገራችንን የቀብር ሥነ ሥርዓት እያፋጠኑ የሚገኙት እነዚህ የቀን ጅቦች ናቸው።
ወያኔ የዘራው ትልቁና መሠረታዊው ችግር የአገር ብሔራዊ ስሜትን ማጥፋቱ ነው። ከዚህ በተያያዘም ሰብዓዊነትን ከአገር አጥፍቷል። በምትኩ የተስፋፋው ዘረኝነት በወንዝ ልጅነትና በጎጥ፣ በቋንቋና በቤተሰብ መሳሳብ የጥቅም ትስስርን አንግሦ ጥቂቶች በሀብትና በሥልጣን ሽቅብ ሲመነደጉ አብዛኛው ሕዝብ እንጦርጦስ እየወረደ ነው። ወያኔ ዘረኝነትን በማስፋፋት ብቻ አልተወሰነም። ለሰው ልጅ ማኅበራዊ እንስሳነት እንደ አያያዥ ስሚንቶ ይቆጠሩ የነበሩ ኃይማኖትን፣ ባህልን፣ የሞራል ዕሤቶችን፣ መተሳሰብን፣ መፈቃቀርን፣ መቻቻልን፣ አብሮ መብላት መጠጣትን፣ … በጥቅሉ አንድን ሰው ሰው ሊያስብሉት የሚችሉ ሰብዓዊና ተፈጥሯዊ ክሮችን በጣጥሶ አንድያውን ሁላችንንም እንደራሱ ዐውሬ እያደረገን ነው። ከዚህ በአገር ደረጃ ከታወጀብን የጥፋት ውርጅብኝ ለማምለጥ የምንውተረተር ዜጎች በጣም ጥቂቶች ነን። ዛሬ የብዙ ሰው መፈክር “ጅብ ከሚበላህ በልተኸው ተቀደስ” ሆኗል። አንድ ማስታወቂያ ነበር – “መጀመሪያ ራስህን አድን ለጫማው በኋላ ይታሰብበታል” የሚል። እኛም “‹ሀ› ራስህን አድን” በሚለው የራስ ወዳድነት መርህ እየተመራን አንዳችን አንዳችንን በልተን ልንጨርስ የቀረን ጊዜ ኢምንት ነው። በጩቤ አለመተራረድ ብቻውን ከአይሲስነት ተፈጥሮ ነፃ አያወጣም። “እሳት ካየው ምን ለየው” ነውና በምንም ይሁን በምን የዘመናችን የጭካኔ መገለጫ አይሲስ ሆኗልና ነጋዴዎቻችንና ጃዝ ባዮቻቸውም የንግዱ ዘርፍ አይሲስ ናቸው – ሥውር አራጆች።
ኑሮ በአዲስ አበባ ምን ይመስላል? ሰዎች ለምንና በምን ብልሃት፣ እንዴትስ ብለው በሀብት ይከብራሉ? ብዙኃኑስ ለምን በሀብት ይደኸያሉ? የአገራችን የሀብት ክፍፍል ምን ይመስላል? አብሮ መኖር ሲቻል መጠፋፋትን ምን አመጣው?
በአሁኑ ወቅት “አገራችን ወዴት እያመራች ነው?” ብሎ መጠየቅ ሞኝነት ይመስለኛል። ይልቁንስ “በጉዞዋ የት ደርሳለች? በብርሃን ፍጥነት እያስነካችው ያለችውን ጉዞ ጨርሳ ወያኔና ታሪካዊ ጠላቶቿ ወዳቀዱላት የመጨረሻ ግብ ለመድረስ ምን ያህል ጊዜ ይቀራታል?” ብሎ መጠየቅ ይመስለኛል አግባብ የሚሆነው። እንጂ ዕድሜ ለወያኔ ካሣለፍነው የሃያ አራት ዓመታት የጥፋት ጉዞ በመነሣት ወዴት እያመራን እንደሆነ ቁልጭ ብሎ የሚታይ ጉልህ ክስተት ነው።
በአዲስ አበባ ስል በመላዋ ኢትዮጵያ እንደማለትም ቢቆጠርልኝ ደስ ይለኛል። ለውጥ ሊኖር ቢችልም እንኳን ያን ያህል የጎላ አይደለምና። እናም በአገራችን ኑሮ በአሁኑ ወቅት እጅግ የሚሰቀጥጥ መሆኑን በመጠኑ እንመልከት።
በደመወዝ ብቻ መኖር ከቀረ ብዙ ጊዜ አለፈን። ደመወዝ ስልህ ደግሞ ይግባህ – የመንግሥትንና በሲፒኤ ደንብ የሚተዳደሩትን ማለቴ ነው። ትላልቅ ደመወዞችን አይመለከትም። በዓለም አቀፍ ደረጃ የሚከፈላቸው አሉና እነሱ የኑሮ ግርፉና ሰቆቃው አይነካቸውም።
በአሁኑ ወቅት የዕቃዎች ዋጋ አይቀመስም። ሠራተኞች ከወር ወር መድረስ ስለማይችሉ ብዙዎች በተራድዖና በልመና እንዲኖሩ ተገደዋል። ዕቃዎች ስልህ የመብል ውጤቶችን ለማለት ነው። አንድ የመንግሥት ወይም የግል ድርጅት ተራ ሠራተኛ በሚያገኘው ደመወዝ ሌላውንና ለዘመኑ እንደቅንጦት የሚቆጠረውን ቤት መሥራትንና ማሳደስን ተዉትና የምግብ ፍጆታውን እንኳን መሸፈን አይችልም – ሌላ የጎን ገቢ ካልተጨመረበት። “ሽምብራ ቆርጥሜ የሠራሁት ቤት” ይባል የነበረው ምሳሌያዊ አነጋገር አሁን የለም – ሽምብራም ከጤፍ በልጦ ተወዷል። በዚያ ላይ ሽምብራም ቆርጥም ባቄላ ከደመወዝህ ቤሣቤስቲን ተርፎህ ለክፉ ቀን አታስቀምጥም። ሲጀመር ኑሮህ በብድርና በዕዳ የተወጠረ እንጂ ከሽሮና ከጎመን ያለፈ አታስብም – ለዚህም ከበቃህ ታድለሃል። ዱሮ በአሥርና በአሥራ አምስት ብር ይገዛ የነበረው ሳልቫጅ ሸሚዝ ራሱ ዛሬ ከብር 130 በላይ ነው – በዚህ ዋጋ በቀደምለት እኔ ራሴ ስለገዛሁ ኅያው ምሥክር ነኝ – ለዚህ መብቃቴም ያስጨበጭብልኛልና እባካችሁን አጨብጭቡልኝ፤ የቢሮ ሠራተኛ – በሙስና ያልተዘፈቀ ማለቴ ነው – ሣልቫጅ ከመግዛት እንኳን አቅም ካነሰው ዓመታት ተቆጠሩ። ዛሬ ሳልቫጅ ራሱ ለመለስተኛ ሀብታሞች መዘነጫ ሆኗል። የኔ ቢጤ ሠራተኛ አዲስ ሸሚዝና ጫማ ለመግዛት ዕቁብ መግባት ይኖርበታል። በሌሎች ያደጉ ሀገራት በአፍሪካም ጭምር አንድ እኔን መሰል ለ20 እና ለ30 ዓመታት አገሩን ያገለገለ ባለ ሁለተኛ ዲግሪ ችግሩ ቤትና መኪና ሣይሆን ሌላ ነው። እኛ ግን ምን ቀምሰን እንደምናድር የምንጨነቅ የነጋዴና የወሮበላ መንግሥት የግዳይ ሰለባዎች ነን። ቆም ብለው ሲያስቡት ያሣዝናል። ይህን የኑሮ ውድነት ለመቅረፍ ታዲያ ብዙ ዜጋ አግባብ ባልሆነ መንገድ ገንዘብ ለማግኘት አቅሉን ስቶ ሲራወጥ ታዩታላችሁ። ድህነት መጥፎ ነው። ድህነት ከኃይማኖትና ከጨዋ ባህል ያወጣል። ድህነት ዐውሬ ያደርጋል። ድህነት ያባልጋል።
ነጋዴው እሳት ሆኗል። የኢትዮጵያ ነጋዴ ዓይንም፣ ጆሮም፣ ልቦናም የለውም። የለዬለት ዕውር ነው፤ የለየለት ደንቆሮ ነው። የንግድ ጽንሰ ሃሳብም የለውም፤ ምክንያቱም ወደ ንግድ የሚገባው የፊደል ዘሮች አልገባው እያሉ ሲያስቸግሩት እንጂ በትምህርትና በልምድ ዳብሮ አይደለም። ብዙው ነጋዴ በአቋራጭ መክበርን እንጂ በሕጉ መሠረትና የሕዝቡን ኢኮኖሚያዊ አቅም ባገናዘበ ሁኔታ አይደለም። የሀገሪቱም ሕግ ሕግ-አልባነት በመሆኑ ማንኛውም ኅሊናቢስ ወንበዴ ወደሀብቱ የሚያደርገው ጉዞ የተቃና ነው። የመንግሥት ተብዬው ባለሥልጣናትም ከማይማን ነጋዴዎች ጋር እየተመሣጠሩ ሕዝቡን ባልተወለደ አንጀት ይገርፉታል። ማይም ባለሥልጣናትና ማይም ነጋዴዎች በእከክልኝ ልከክልህ የጥቅም ትስስር ሀገሪቷንና ሕዝቧን ወደ ገደል እየከተቷቸው ነው። አንድም ሃይ ባይ ሳይኖር ኢትዮጵያን የመሰለች የድንቅ ታሪክ ባለቤት እየጠፋች ነው። ማን ይድረስላት?
ዱሮ ስንጥቅ ትርፍ ሲባል እንሰማ ነበር። “እገሌ ስንጥቅ ትርፍ አተረፈ” ይባል ነበር። ዛሬ ግን እንደዚያ ብሎ ነገር የለም። ስንጥቅ ማለት እንግዲህ ግማሽ በግማሽ ለማለት ይመስለኛል – ለምሳሌ መቶ ብር የተገዛን ዕቃ 150 ወይም ግፋ ቢል 200 ብር የመሸጥ ያህል። አሁን ግን መቶ ብር የተገዛን ዕቃ ጊዜ እየጠበቁና ሆን ብለው እያስወደዱ ከአምስትና ስድስት ሺህ ብር በላይ ካልሸጡ የነገዱ የማይመስላቸው አይሲሶች ተፈጥረዋል። ስለዚህም አንድ ሰው ንግድ በጀመረ በጥቂት ሣምንታትና ወራት ውስጥ አንቱ የተባለ ዲታ ይሆንና መኪና እንደሸሚዝ ሲለዋውጥ ታየዋለህ፤ በዚያ ላይ ወያኔያዊ የደምና የአጥንት ንክኪ ካለው ሣምንት ቀርቶ ደቂቃዎችም ሳይፈጅበት ቀጭን ጌታ ይሆናል – ትምህርት ዕርሙ በሆነበት ድባብ ውስጥ ለሚኖር አንድ ማይም ዘረኛ ደግሞ ይህ ዓይነቱ በሀብት የመወንጨፍ ዕድል ከባድ አይደለም። ዋናው ነገር አዕምሮን የማሳመን ጉዳይ ነው። የኃይማኖትና የግብረገብ ትምህርት የሌለው፣ የይሉኝታና የሀፍረት ስሜት ጨርሶ የሌለው፣ ከአንዲት ትንሽ ጎጥ በዘለለ ማሰብ የማይችል “ሰው” አጭበርብሮና አታልሎ ብቻም ሣይን ገድሎና አሥሮም ቢሆን ቢከብር የሚጠይቀው ኅሊና ወይም ምድራዊ ሕግ የለም። ሁሉም እርሱን ለመርዳት የቆመ ነውና። ሰው ደግሞ በተፈጥሮው ከኅሊናው ጋር ከተቆራረጠ የመጨረሻው ዐውሬ ነው የሚሆነው። በሁሉም መንገዶች ተጉዞ ወደሚፈልገው ማማ መውጣት ነው ጥረቱ።
ትናንት ሰላጣ አማረኝ። ብዙውን ጊዜ ጥቃቅን የምግብ ፍጆታዎችን ከማንጠግቦሽ በተጓዳኝ እኔም እገዛለሁና ወደጉሊት ወጣ አልኩ። ገበያው በአንጻራዊ አነጋር ከቀደሙት የጾም ወራት አሁን ደህና ነበር ማለት እችላለሁ – በተለይ በአንዳንድ ዕቃዎች። ቀይ ሽንኩርት በኪሎ 16 ብር፣ አንዲት የጠወለገች ሙትቻ ሎሚ በአንድ ብር ከሃምሣ፣ ቲማቲም በጣም ቀነሰ ተብሎ ኪሎውን በ8 ብር፣ ቃሪያ (በጣም ጦፏል!) ግማሽ ኪሎ በ23 ብር፣ ሃቱም የተባለውን አንድ ሊትር ዘይት 78 ብር፣ አንዲት እግር ሰላጣ በ8 ብር ገዝቼ ፀጉሬን እየነጨሁ ወደቤቴ ተመለስኩ። ሰላጣ ለመብላት ስንት እንዳወጣሁ እናንተው አስሉት – ዘይቱ እርግጥ ነው ትንሽ ጊዜ ይቆያል። ይህን ኑሮ የትኛው የመንግሥት ሠራተኛ ችሎ ይኖራል? ሥጋንና ወተትንማ ጭራሽ አታስቡት፤ ከጥቂት ጊዜ በኋላ በሉካንዳ ቤት ስናልፍ የተሰቀለን ሥጋ በሱቲ ጨርቅ እየሸፈኑ ገልጠው ለማሳየት ብቻ ሳያስከፍሉን የሚቀሩ አይመስሉኝም።
ልብ አድርጉ – እኔ ባለደህና ደሞዝተኛ ተብዬው ለልጆቼ ብርቱካንና ሙዝ አንጠልጥዬ መግባት ካቆምኩ ዓመታት አልፈዋል – እንዳልዋሽ እጅግ አልፎ አልፎ በወረት ካልሆነ በስተቀር የምነግራችሁ እውነቴን ነው። አንዲት ኪሎ ሙዝ 14 ወይ 15 ብር፣ አንድ ኪሎ ብርቱካን ከብር 22 በላይ ገዝቼ እንዴት እችላለሁ? ደግሞስ አንድና ሁለት ኪሎ መች ይበቃንና ወስፋት ላጩህ? ለመሆኑ ስንቱ ቤተሰብ ነው ሥጋና ወተትን የመሰሉ አልሚ ምግቦችን በቅጡ የሚመገበው? ብዙው ቤተሰብ ሥጋን የሚያውቀው ሃሊዮ ኮሜት በሰባ ስድስት ዓመት አንዴ እንደምትታየው ሁሉ በዓመት ሁለቴና ሦስቴ ብቅ በሚሉ ፋሲካን የመሰሉ ዐውዳመቶች ነው። ሞተናል እኮ። ገድለውናል እኮ። እንዳሰቡት ሆነንላቸዋል እኮ። ዕቅዳቸው እኛን ማጀታችን ውስጥ ወሽቀው ስለምንቀምሰውና ስለምንልሰው እንድንጨነቅ ማድረግ አልነበረም? ታዲያስ! እናሳ አልተሣካላቸውምን? አለመረገማችንን የማናምን ከዚህም ባለፈ እኛ ኢትዮጵያውያን ዕድለኞች መሆናችንን አዘውትረን የምንናገር ብዙዎች ልንሆን እንችላለን – ነገር ግን ሆዱን እንኳን መቻል በሚያቅተው ማኅበረሰብ መካከል መገኘት ከመረገሞችም በላይ መሆኑን ልብ ልንል ይገባል። የሰው ልጅ በሥልጣኔ የትና የት ደርሶ፣ “አውሮፓውያንና አሜሪካውያን ከማዕዳቸው ተርፎ የሚጣለው የዕለት ምግብ ለአፍሪካውያን የዚህን ያህል ጊዜ ቀለብ ይሆናል” እየተባለ ሲነገር ትንሽም የማይቆጫቸው መሪዎች ያሉን አሳዛኝ ሕዝቦች ነን – አፍሪካውያን በጠቅላላው። የኛ ደግሞ ከሁሉም በባሰ ቆሎም ባቅሙ አርሮብን፣ ልብሳችን በላያችን ላይ አልቆ፣ አጥንታችን አግጥጦ፣ … እንዲሁ ኑሮ ብለነው እንንጠራወዛለን። ሞታችንን በቁማችን ጨርሰን በትንሽ በሽታ ህቅታችን ስትወጣ መቼም ወግ ነውና ሞቱ ተብለን ድንኳን ተጥሎ ይለቀስልናል።
እርግጥ ነው የፊት ለፊት ስዕላችን አሁን ከምለው ለየት ያለ ሊመስልና እኔንም እንዳጋነንኩ ሊያስቆጥርብኝ ይችል ይሆናል። እኔ እያወራሁ ያለሁት እውነተኛውን በወያኔ ሚዲያ ግን የተሸፈነውን አገራዊ ማንነት ነው። የኔን ሕይወት፣ የወንድምና እህቶቼን ሕይወት፣ የአብዛኛውን ሕዝብ መሪር ኑሮ ነው እየተናገርኩ ያለሁት። እንጂ የተመቸው ጥቂት የማይባል ዜጋ መኖሩን አውቃለሁ። ግን ያም ምክንያት አለው። የተሻለ ደሞዝ ያላቸው፣ በሥራቸው ምክንያት እጅ መንሻ የሚያገኙ፣ ቤት የሚያከራዩ፣ ቤትና ዕቃ የሚሸጡና የሚለውጡ፣ ከዲያስፖራው ገንዘብ የሚላክላቸው (እኚህኞቹ ቀላል ቁጥር አይደለም ያላቸው)፣ መኖሪያ ቤታቸውን ወደአነስተኛ የንግድ ቤትነት ለውጠው እንደነገሩ የሚውተረተሩ፣ በስርቆት፣ በማጭበርበርና በሙስና ትልቅ ገቢ ያላቸው፣ … ወገኖቻችን መሬት ላይ ከሚታየው ህንፃና መንገድ ጋር ተደማምረው እውነተኛውን አገራዊ ምስል ለጊዜው ሊደብቁት ቢሞክሩም እስከወዲያኛው ግን ሸፍነው ሊያቆዩት አይችሉም። ከነዚህ ከጠቃቀስኳቸው የጎን ገቢዎች የራቀው ተራው ገበሬ፣ መምህሩ፣ የመንግሥት (የቢሮ፣ የጽዳት፣ የጉልበት፣ የጥበቃ …) ሠራተኛው፣ ተራው ወታደር፣ ከጉቦ ጋር ብዙም የማይወዳጀው የፖሊስና የፀጥታ ሠራተኛ፣ ሥራ አጡ ወገን፣ ህጻኑ፣ ሽማግሌው፣ ለማኙ፣ በረንዳ አዳሪው፣ ሴተኛ አዳሪው፣ ወዘተ … እንዴት እንደሚኖር ብታዩ በኢትዮጵያ ያጡ የነጡ ድሆችን ሣይሆን በምሥኪኖች ላብና ደም የከበሩ ሀብታሞችን ደኅንነት ለመጠበቅ ብቻ ተግቶ የሚሠራ ሥውር ምናልባትም መንፈሣዊ ኃይል መኖሩን እንድታምኑ ትገደዳላችሁ። በሌላ በኩል ደግሞ በዚህ ሁሉ ተነግሮ በማያልቅ የኑሮ ውጣ ውረድና መሪር አገዛዝ እያረረና እየነደደ የሚገኝ ሕዝብ ርስ በራሱ ተባልቶ እንዳያልቅ ለመርዳት ሲል ፈጣሪ ጓዙን ጠቅልሎ ኢትዮጵያ ውስጥ የከተመ እስኪመስለን ድረስ በፈጣሪ ጥበቃ እንድንገረም የሚያደርግ ሁኔታ እንታዘባለን – የዕንቆቅልሽ ምናውቅልሽ አገር፤ ኬንያ ወይም ደቡብ አፍሪቃ እኮ ቀን በቀን ነው ሰው የሚዘረፈው። እዚህ የምናየው ትግስት ልዩ ነው። ራሱ እየተራበ የሰው ወርቅ ሲጠብቅ የሚያድር ዜጋ የምታገኘው ኢትዮጵያ ውስጥ ብቻ መሆን አለበት፤ ራሱ በጠኔ እየተሰቃየ ሀብታሞችን አንደላቅቆ የሚያኖር ሕዝብ የሚገኘው በአፍሪቃ ቀንድ ኢትዮጵያ ውስጥ ብቻ ይመስለኛል። በ”አንተ ታውቃለህ” እና “አንተ ያመጣኸውን አንተው መልሰው” ነባር ጸሎት የሚኖር ብቸኛ ሕዝብ ቢኖር የኛው ሕዝብ መሆን አለበት። ይሁንና ግን ጊዜ የማይወልደው ክስተት የለምና እየተንተከተከ ያለው ማኅበራዊ ቀውስና ፍትህ አልባው የሀብት ክፍፍል አንድ ቦታ ከተነፈሰ መመለሻ የለውም። “ማን እየኖረ ማን ይሞታል?” ከሚል አሳማኝ መነሻ ሆድ የባሰው ሁሉ አገሪቱን የሁከት ማዕከል እንዳያደርጋት ያሰጋል። ሊቢያና ሦርያም ከብዙ አሥርት ዓመታት ግፍና በደል በኋላ ነው የአሁኑን አስጠሊታ ቅርጽ ሊይዙ የቻሉት። እናም መፍራት ደግ ነው። “አይመጣምን ትተሽ ይመጣልን በያዝሽ” ነው ነገሩ። የናቁት ማስረገዙ፣ የጠሉት መውረሱ፣ … ከጥንትም ነበር።
የሕዝባችንን ቁስቁል ለመረዳት እስኪ ለአብነት የአውሮፓን ካምቦሎጆዎችንና የአገራችንን ካምቦሎጆዎች በእግር ኳስ ግጥሚያዎች ጊዜ ተመልከቱ። የአዲስ አበባ ኳስ ሜዳ በምን ዓይነት ደቃቃ ሰዎች እንደሚሞላ፣ የአውሮፓውያኑ ደግሞ በምን ዓይነት ሰዎች እንደሚሞላ ታዘቡና የደረስንበትን የድቀት ደረጃ አስተውሉ፤ በአለባበስ፣ በሰውነት ይዞታ፣ በቁመት፣ በወርድ … በሁሉም አስተያዩ። ሰው ምግቡን ይመስላል። አመጋገብ ብዙ ትርጉም አለው፤ በአስተሳሰብና አመለካከት፣ በፍልስፍና፣ በሥነ ልቦና፣ በአካላዊ ዕድገትና ጤንነት፣ ወዘተ … ምግብ ወሳኝ ነው። ካለተመጣጣኝ ምግብ ጤናማ አዕምሯዊ ዕድገት አይገኝም፤ ካለተመጣጣኝ ምግብ ቁንጅናና ውበት የለም። ካለተመጣጣኝ ምግብ ትምህርት መማርም የሚታሰብ አይደለም። ሆድ ባዶ ሆኖ ወይም አሸርባሸር በልቶ ትምህርት ወደአዕምሮ ይገባል ማለት ዘበት ነው፤ የሆዱን ጥያቄ ባግባቡ ያልመለሰ ተማሪ አካሉ ክፍል ውስጥ ይቀመጥ እንደሆነ እንጂ መንፈሱ ወደምናባዊ ኩሽናዎች መሸፈቱ አይቀርም። ዝም ብለን “ሐበሻ ምቀኛ ነው” ብንል ዋጋ የለውም። ይልቁንስ ከአመጋገባችን አንጻርም ችግር ይታየኛልና ይህን የተጣመመ የኑሮ ገመናችንን ለማስተካከል ልዩ ኮሚቴ ካሁኑ ተቋቁሞ ይሰብበት። (ይቺ ጤፍ የምትባል ነገር የምቀኝነት መንስኤ ንጥረ-ነገር ሳይኖራት እንደማይቀር የሚናፈሰው ወሬም ቢጠና አይከፋም። ማን ያውቃል?)
በሌላ አቅጣጫ ጥቂቶች መሬትን ተጠይፈው ጮቤ ይረግጣሉ። ከኛ አላግባብ በሚዘርፉት ገንዘብ አዲስ አበባ ምድር ቃጤ ስትሆን ታመሻለች፤ ታድራለችም። እኔን እየራበኝና አብዛኞቹ መሠረታዊ ፍላጎቶቼ ታፍነው እነዚህ ጥቂቶች ብሩን ለየምናምኑ ሲረጩት ይታያሉ – ካለድካም የመጣ ገንዘብ ደግሞ እሳት ላይ የወደቀ ቅቤ እንደማለት ነው። ሀብታሞች ቅጥ አጡ – የኛ ድህነትም ቅጥ አጣ። በአገራችን ሁለት ፍጹም ተቃራኒ ጫፎች ተፈጥረው ለዳኝነት ብቻ ሣይሆን ለታዛቢም ሳይቀር አስቸገሩ። ሀብታሙ እንዴት እንደሚኖር ስናይ ድሃው ደግሞ ቆሼ ተራ ለፍርፋሪና ለሙዝ ልጣጭ እንዲያ በሺዎች እየተራኮተ ሲታይ የገነትንና የሲዖልን ኅልውና እስክንረሳ ድረስ እንደመማለን – ገነትንም ሲዖልንም በተግባር የምናያቸው ያህል ይሰማናልና። ሙስናው ደግሞ ጣሪያ ያለው አይመስልም። በደሞዙ ከእኔ ታች የሆነ አንድ የቀበሌ አስተዳደር ሥራ አስፈጻሚ ወር እስከወር ከቡና ቤቶች እንደቆርኪ ተጠርጎ ነው ውድቅት አካባቢ ወደቤቱ እየተወላገደ የሚሄደው። የመንግሥት ባለሥልጣናት ደሞዛቸውን አያውቁትም። ከትንሹ እስከ ትልቁ ባለሥልጣን ያለሙስና ቢኖሩ እስትንፋሳቸው ቀጥ የሚል ይመስላቸዋል፤ ይላልም።
ሙስና የአገራችን የደም ዝውውር ሆናለች። ካለሙስና የሚኖር የመንግሥት የሥራ ኃላፊ አለ ማለት ያስቸግራል፤ ካለም በድህነት እየተሰቃየ በመኖር የበይ ተመልካች ለመሆን መርጧል ማለት ነው – ጥሩና አዋጪ ምርጫ። የአብዛኛው የወቅቱ ምርጫ ግን በተገኘው አጋጣሚ ሁሉ መክበር ነው። ጨረታና ግዢ ደግሞ ዋናዋ የግል ብልጽግና ማሳለጫ ናት። በቡድንም ይሁን በግል አገርን መዝረፍና በአቋራጭ መክበር የብዙዎች ምኞትና የዕለት ተለት ድርጊትም ነው። ምን ይሉኝ የለም። የሚሠሩ ነገሮች ደግሞ ብዙዎቹ የጥራት ደረጃቸውን አያሟሉም። የጨረታ አሸናፊዎች ከዘርና ከሙስና ጋር በቀጥታ የተያያዙ ናቸው – ጥራትና አመክንዮ፣ አገርና ሕዝባዊ ወገንተኝነት ዋጋ የላቸውም። ሥራዎች ተጠናቀው ርክክብ ይፈጸማል። በሙስና የተሠራ አንድ የግንባታ ዕቅድ ወይ መንገድ በትንሽ ጊዜ ውስጥ ፍርስርሱ ይወጣና ኪሣራ ብቻ ይሆናል – ያኔ ጠያቂም ተጠያቂም የለም። ለምን ቢባል ማን ማንን ይጠይቃል? ሁሉም ሌባና ራስ ወዳድ ነው፤ ሁሉም በተመሳሳይ የሙስና ቁስል የነፈረ ነው፤ ቂጥኛም ውርዴን፣ ውርዴም ቂጥኛምን የመጠየቅ ሞራላዊ ብቃትም ሆነ ሕጋዊ መደላድል የለውም – በክት ለበክት እየተጠቃቀሰ ይጠቃቀማል፤ አገርና ሕዝብ ግን ያለቅሳሉ።
በመቶ ሺዎች ወጪ ሊሠራ የሚችል አንድ ግንባታ ብዙ ሚሊዮኖች ፈሰውበትም ከሚፈለገውና ከሚጠበቀው የጥራት ደረጃ እጅግ የወረደ ነው። በእንጨት ባላ የተደጋገፈ አንድ የሕዝብ ትምህርት ቤት አውቃለሁ – ባለ አራት ፎቅ። እንዲያ ስንጥቅጥቁ የወጣው ደሞ ገና ከርክክቡ ቀደም ብሎ ነው። ተማሪዎቹ እንዳይወድቁ ወይም ከናካቴው እንዳይደረመስባቸው ያሰጋል – በዚያ ትምህርት ቤት የዘመዴ ልጅ ይማራልና እኔም በዓይኔ አይቼ ተገርሜያለሁ። ለአገር ማሰብና መቆርቆር ቀርቷል። የትም ፍጪው ነው የነገሠው። አገርህ በቁም ሞታለች። ሐበሻ በያለህበት ዕርምህን አውጣ። ነገር ግን “ፀጉራም ውሻ አለ ሲሉት ይሞታል” ነውና ተረቱ ያለች ትመስላለች – ሞታ ሳለች። ሞት ዓይነቱ ብዙ መሆኑን ተረዳ።
ወደሚሰቀጥጠው ኑሯችን ልመልስህ፤ ያንተ ኑሮ የተያዘለት ሊሆን ይችላል – ማለፊያ ኑሮ ማለቴ ነው። ቢሆንም እኛም ያንተው ወገኖች ነንና እሮሮኣችንን ስማልን፤ እዘንልንም። ከአንተ በላይ ለኛ ማን ሊያዝንልን ይችላል? እንደዱሮው በተወሰነ ጊዜ ጫማ መግዛት፣ ልብስ መግዛት፣ የቤት ዕቃ መቀየር፣ ወዘተ፣ ዛሬ በተራው ሠራተኛ ዘንድ የሚታሰብ አይደለም። ገንዘብ ልታገኝ ትችል ይሆናል። ዘመድም ሊሰጥህ፣ ጓደኛም ሊለግስህ ይችል ይሆናል። ነገር ግን የሚሰጥህ የገንዘብ መጠን በመቶ ሺዎችና በሚሊዮን የሚገመት ካልሆነ በስተቀር በመቶዎችና በጥቂት ሺዎች የሚገመት ከሆነ ከተወሰኑ ቀናት የምግብ ፍጆታ ውጪ የሚያልፍ አይደለም። የገንዘቡን የመግዛት አቅም ምች አጠናግሮት ተሽመድምዷል። ለዚህም ይመስለኛል ብዙዎች በሚያገኙት መጠነኛ ገንዘብ ምንም ዓይነት ሻል ያለ ነገር መሥራት እንደማይችሉ ከመገንዘብ አኳያ እምብርታቸውን ወትፈው ሌት ከቀን ሲጠጡና ሲሰክሩበት የሚታዩት – ይህ ደግሞ እውነተኛ የደስታ ስሜት መገለጫ ሣይሆን የተስፋ መቁረጥ ስሜት የወለደው ጊዜያዊ መጠለያን የመሻት ፍላጎት የፈጠረው ነው። እና መጠጥ ቤቶች ሞልተው ቢታዩ አገር አማን ነው ማለት አንችልም። በነገራችን ላይ ይህን መሳይ በሁሉም ረገድ የወደቀና ከሆዱ ባለፈ ምንም ነገር ማሰብ የማይችል ሕዝብ መግዛት ለአምባገነኖች ሠርግና ምላሽ ነው። የተማረና የሠለጠነ፣ በሀብትም በትውፊትም የዳበረ ማኅበረሰብ ገዢዎቹን ብዙ ጥያቄ ይጠይቃል። መብቱን ያስከብራል። እንደኢትዮጵያ ባሉ አገሮች የሚገኙ ማይም ገዢዎች ግን ሕዝቡ እንዳይነቃና ከዕለት ጉርሱ ባለፈ ሀብት እንዳይኖረው በማድረግ እንደእንስሳ እየገረፉ ይገዙታል። የኛ ግን ባሰና ለዕለት ጉርስና ለዓመት ልብስም መድረስ አቃተን። ፈራጁ ኃያል አምላክ በመጨረሻው የድርሻቸውን አይከለክላቸውም። በዚያ ብቻ እንጽናናለን።
ሰዎች ሀብታም የሚሆኑባቸው የተለያዩ መንገዶች አሉ። አብዛኞቹ ግን ሕገወጥ