“እንደኔ እንደኔ የዚህ ሀገር ችግር ከፖለቲከኞቹ በላይ ሃይማኖቶቹ መሪዎች ናቸው ብዬ አስባለሁ” (መጋቢ ሀዲስ እሸቱ)

“እንደኔ እንደኔ የዚህ ሀገር ችግር ከፖለቲከኞቹ በላይ ሃይማኖቶቹ መሪዎች ናቸው ብዬ አስባለሁ”
(መጋቢ ሀዲስ እሸቱ)

እዚህ ሀገር ላይ ስኖር እንደ ሶስት ሰው ሆኜ ነው የምኖረው፡፡

እንደ ኢትዮጵያዊነቴ አስባለሁ፡፡ እንደ ሰውነቴ አስባለሁ፡፡ እንደ እምነት ተቋም ሰውነቴም አስባለሁ፡፡ እንደ ሶስት ሰውነት ለማሰብ ግን ሀገርና ህዝብ ያስፈልጋል፡፡ ያለ ሀገር መኖር አንችልም፡፡

አለምን የሚያጠፏት ተስፋ የቆረጡም ገደብ ያለፈ ተስፋ የሰነቁም ናቸው፡፡ መንግስት እንደው ተቀያያሪ ነው፡፡

በሊቢያ የመጨረሻው ፕሬዚዳንት ሙሐመድ ጋዳፊ ሆኑ፡፡ የኢራቁ ደግሞ ሳዳም ሁሴን፡፡ ሶርያ የምትባለው ሀገር ለመቀጠሏ ምንም ማረጋገጫ የለንም፡፡ ጎረቤቶቻችንም እየታመሱ ነው፡፡ እዚህ እየተፈጠረ ያለው ችግርም ከነዚህ ሀገራት ባልተናነሰ አስጊ ነው፡፡ ፖለቲካዊ አመለካከትን እንደ መለያያ ምክንያት ማቅረባችን ተገቢ አይደለም፡፡ የቋንቋ ልዩነታችንን፣ የሃይማኖት ልዩነታችንን በምክንያት ማቅረብ ለድክመቶቻችን ሽፋን እንደ ማበጀት ነው፡፡

4 ኪሎ ላይ ከሃጎስ ጋር የተጣላ ሰው፤ እስከ አድዋ፣ ሽሬ አክሱም ድረስ መሣደብ፤ ከሁሴን ጋር የተጣላ እስልምናን መስደብ ነውረኝነት ነው፡፡ በአንድ ቶሎሳ ምክንያት በሚሊዮን የሚቆጠር ኦሮሞ መስደብ፣ በአንድ ሃጎስ ምክንያት ሙሉ ትግሬን መስደብ፣ በአንድ የጎንደር ተወላጅ ምክንያት ሚሊዮን ጎንደሬን መስደብ ያልተገረዘ አንደበት ውጤት ነው፡፡

እንደኔ እንደኔ የዚህ ሀገር ችግር ከፖለቲከኞቹ በላይ ሃይማኖቶቹ ናቸው ብዬ አስባለሁ፡፡ የእምነት ተቋማት መስራት ያለባቸውን ስራ አልሠሩም፡፡ መንግስት ልማት ሲል እኛም ልማት እያልን ነው የምናስተጋባው፡፡

ሃይማኖቶች ለአገሪቱ የለማ ጭንቅላት ነው ማፍራት ያለባቸው እንጂ መንግስት ዶማ ሲያነሳ ዶማ እያነሱ፣ ህንጻ መገንባት አይደለም ድርሻቸው፡፡ ሁሉም ሃይማኖቶች ድህነትን ከመቀነስ ይልቅ ሃጢአትን መቀነስ ላይ ቢተጉ መልካም ነው፡፡ እነሱ የሃይማኖት ስራቸውን አለመስራታቸው ነው ይህቺን ሃገር ለዚህ ችግር ያጋለጣት፡፡

ድሮ እርቅና ሠላም ለማምጣት ሃይማኖቶች ወሳኝ ነበሩ፡፡ “ፍቅር እስከ መቃብር“ ላይ እንኳን ሁለቱ ፊት አውራሪዎች ሲጣሉ ካህናት ናቸው ያስታረቁት፡፡ ይሄ የቀድሞ ጊዜ የገሃዱ አለም ነፀብራቅ ነው፡፡ ዛሬ የእምነት ተቋማት በዚህ መደብ ውስጥ የሉበትም፡፡ ራሳቸው የሠላምና የእርቅ ተቋም መሆን ስላልቻሉ ነው፤ አጥፊን መገሠፅና መቆጣት ያልቻሉት፡፡ የመንግስቱ ንዋይ መፈንቅለ መንግስት ሲከሽፍ፣ የፓትሪያርኩ ሚና ወሳኝ ነበር፡፡ ወታደሩ መሳሪያውን የዘቀዘቀው በፓትሪያርኩ ተግሣፅ ነበር፡፡ አሁነ ግን ተቋማቱ በራሳቸው ቅቡልነት የሌላቸው ሆነዋል፡፡ የራሳቸውን ስራ ትተው የመንግስት ስራ እንስራ እያሉ ነው፡፡ ልማት ሲባሉ ሰው ማልማት ትተው፣ ሱቅና ህንፃ የመገንባት ፉክክር ውስጥ ነው የገቡት፡፡ እንደ እኔ የእምነት ተቋማት፤ ድንጋይ መቆለልና ሲሚንቶ ማቡካታቸውን አቁመው የሰው ጭንቅላት ያልሙ፡፡
።።።።
(ለአዲስ አድማስ ጋዜጣ ከሰጡት ቃለ መጠይቅ የተወሰደ)
መምህራችንን ቃለ ህይወት ያሰማልን!i